+251-993-818276 akofeda@gmail.com Addis Ababa, Ethiopia

አንደኛው ዓለም ዐቀፍ ጉባዔ /የኒቂያ ጉባኤ/ (ሲኖዶስ) በ 325 ዓ.ም (ክፍል ሁለት)

የኒቂያ ጉባዔ ሂደት
ከተፍፃሜተ ሰማዕት እና ከእለእስክንድሮስ በግል ማውገዝ በኋላ ቅዱስ እለእስክንድሮስ ሦስተኛውን ውግዘት በማህበር በ 318 100 የሚሆኑ የእስክንድርያ እና የሊቢያ ኤጲስ ቆጶሳትን ሰብስቦ የስህተት ትምህርቱን ካስረዳቸው በኋላ በአንድ ድምፅ አውግዘውታል፡፡
በዚህም ወደ ሶርያና አንጾኪያ በመሄድ እለእስክንድሮስ የሰባሊዮስን ኑፋቄ እንደሚያስተምር እና እሱንም ያለ አግባብ እንዳወገዘው የቀድሞ የት/ቤት ጓደኞቹ ለሆኑት ለኒቆሞድያው አውሳቢዮስ እና ለቂሳርያው አውሳቢዮስ በመንገር በእነሱ አካባቢ ትምህርቱን ማስፋፋት ቀጠለ፡፡
በ 322 እና በ 323 ሁለት ጊዜ የእርሱ ደጋፊዎች ተሰብስበው ትምህርቱን በመደገፍ እና እርሱን ከውግዘት በመሻር ትምህርቱን እንዲያስፋፋ ፈቀዱለት፡፡
በትምህርቱም መስፋፋት ከሮም ጀምሮ መላው ዓለም በትምህርቱ ታወኩ፡፡ መምህራን ከመምህራን መነታረክ ጀመሩ፡፡ ይህም ንትርክ ከቤተክርስቲያን አልፎ ለሀገር ጭምር የሚያሳስብ ሆነ፡፡
ንጉሥ ቆንስጠንጢኖስም ይህን ውዝግብ በዲፕሎማሲ እና በሰላም ሊፈታው ቢሞክርም የማይሆንለት ስለሆነ ዓለም አቀፍ ጉባኤ እንዲደረግ ጥሪ አደረገ፡፡
ጉባኤው ‹‹በአንካራ›› እንዲካሄድ ተወሠነ ፤ በኋላ ለመናገሻ መንግሥቱ (ቆስጠንጥንያ) ቅርብ ወደሆነችው እና ለመጓጓዝ ወደ ምታመቸው ‹‹ኒቂያ›› ተዘዋወረ፡፡
318 ኤጲስ ቆጶሳት እና ተከታዮቻቸው ሙሉ ወጪያቸው በመንግሥት ተሸፍኖ በጉባኤው ተገኙ፡፡ እነዚህ ጳጳሳት በንጽሕናቸው/በቅድስናቸው/ የተመሠከረላቸው ገቢረ ተአምራትን የሚያደርጉ ከዘመነ ሰማዕታት ስደት የተለያየ የአካል ጉዳት ደርሶባቸው የተረፉ ነበሩ፡፡ በዚህም ምክንያት (አብዛኞቹ አካለ ጎዶሎዎች) እንደሆኑ ታሪክ ያስረዳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም
20 አርዮሳውያን ፣ አርጌንሳዊያንችና ፈላስፋዎችም በጉባኤው ላይ ነበሩ፡፡
ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤው ከሰኔ 14 -ሐምሌ 25 ነው ሲሉ፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጉባኤው ከመስከረም 21- ህዳር 9 ነው ብላ ታስተምራለች፡፡ (ከቄልቄዶን ጉባኤ በፊት በአንድነት ይህንን ጉባዔ የምንቀበል (የሮም፣ የምስራቅ ኦርቶዶክስ ቤን እና የእህት ቤተክርስቲያኖች) ይህንን ነው ጉባዔ ስለምንቀበል ምርመራ ተደርጎ አንድ ወደ ሚያደርገን ቀን መምጣት ይቻላል)
የጉባኤው ፕሬዝዳንት ንጉሠ ነገሥቱ ሲሆን ሊቃነ መናብርቱ ደግሞ
እለ-እስክንድሮስ – ከእስክንድርያ ቤተክርስቲያን
ኤዎስጣቴዎስ – ከአንጾኪያ ቤተክርስቲያን
ኦስዮስ – የኮርዶቫ (ስፔን)ቤተክርስቲያን ናቸው
ከ 318 ኤጲስ ቆጶሳት በተጨማሪ በኦርቶዶክስ አስተምሮ የጠለቀ እውቀት የነበራቸው ሰዎች ነበሩ ፡- ከነዚህም በዋናነት የሚጠቀሰው የእለእስክንድሮስ ጸሐፊ ቅዱስ አትናቴዎስ ነው፡፡
በጉባኤው ላይ ከተገኙ ኤጴስ ቆጶሳት መካከል በከፊል
የኢየሩሳሌሙ መቃርዮስ
የእንቆራው ማርሴሎስ
የቲቤቱ(ቴባስ) ፓፋንተስ-፤ የሔራቅሊጠሱ ጶጣምን ሁለቱም አካል ጉዳተኞች ነበሩ
የአዲስቱ ቂሳርያ – ጳውሎስ
የኒሲቢው ያዕቆብ – በጳጳስነት ዘመኑ እንኳን የበግ እረኛ ነበር፡፡
የፋርሱ ዩሐንስ
የጎቲክ ቴዎፍሎስ እና ስታራቶፊለስ
ከምዕራብ
የካላበራው ማርቆስ(ኢጣሊያ)
የሊቢያ(ቅርጣግ/ካርቴጅ/) – ሲሲሊየን
የስፔኑ – ሆስየስ የኮርዶቫው
የጉባኤው አጀንዳ
ከእርዮስ የምንፍቅና አስተመህሮ በተጨማሪ ከዛ በፊት የነበሩ እና እስከዚህ ጉባኤ የዘለቁ ቤተክርስቲያንን ሲለያዩ እና ሲያበጣብጡ የነበሩ የተለያዩ ጉዳዮች የዚህ ጉባኤ አጀንዳዎች ነበሩ፡፡
የአርዮስ ኑፋቄ (የምንፍቅና አስተምህሮ) ጥያቄ
የፋሲካ አከባበር
የሜሊጢዮስ ኑፋቄ(መለያየት)
የአብ እና የወልድ አንድነት በአካል ወይስ በሥራ
የመናፍቃን ጥምቀት ናቸው
የጉባኤው ቡድኖች
በትምህርቱ ሚስጢራዊነት እና በወቅቱ ነበረው የትምህርቱ ክብደት ምክንያት በጉባኤው ላይ ሦስት ዓይነት ቡድኖች ነበሩ፡-
ኦርቶዶክሳዊያን፡
እለእስክንድሮስ
ኤዎስጣቴዎስ
ኦስዮስ
ማርሴሎስ
አትናቴዎስ (ዲያቆን)
አርዮሳውያን
አርዮስ
የኒቆሞዲያሱ አውሳብዮስ (የንጉሡ ወዳጅ)
የኒቂያው ቴአግኒስ
የኬልቄዶኑ ማሬስ (በኋላ የተመለሠ)
የኤፌሶኑ ሜኑፋንቱስ
መንፈቀ አርዮሳውያን(መሀል ሠፋርያን)
-የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊው የቄሳርያው አውሳቢዮስ በኋላ ኦርቶዶክሳዊ የሆነ
ክርክሩ
አርዮሳዊያን ፡- ወልድን “ዋሕድ ባሕርየ ምስለ አብ / ከአብ ጋር አንድ ባሕርይ” “Omoousious” የማይል የተወገዘ ይሁን የሚል
የሃይማኖት መግለጫ አቅርበው ተቃውሞ ደርሶባቸዋል፡፡
አርዮስም በጉባኤው ተጠይቆ ከላይ የአርዮስ አስተምሮ የሚለውን ገልጿል፡፡
አርዮስ ፡- ወልድ የጸጋ አምላክ ስለሆነ ስግደት ይገባዋል፡፡
የቅዱስ አትናቲዮስ መከራከሪያ
ወልደ-አብ ኢየሱስ ክርስቶስ መድኃኒት ነው ፤ አዳኛችን ነው፡፡
የሚያድን እግዚአብሔር (አምላክ) ብቻ ነው ፤ መጽሐፍት የሚያስተምሩት ይህንን ነው፡፡
ወልድ አምላክ ካልሆነ እኛም አልዳንም፡፡
በእርሱ መዳናችንን ካመንን ያዳነን እርሱ አምላክ ነው ፤ ፍጡር ማዳን አይችልምና፡፡
አትናትዮስ ፡- ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ አንድ ነው ፡፡ ወልድ ፍጡር ከሆነ ለእርሱ የአምልኮ ስግደት ማቅረብ ባዕድ አምልኮ ነው፡፡
‘ቦ አመ ኢሀሎ’ ወልድ ያልኖረበት ጊዜ የለም ዘላለማዊ ነው፡፡
የአርዮስ ደጋፊዎቹ/መንፈቀ አርዮሳውያን/ ወልድን Omo-ousious (ከአብ ጋር አንድ ባሕርይ) በማለት ፈንታ Omoi-ousious (የወልድ ባሕርይ ከአብ ባሕርይ ጋር ተመሳሳይ) ነው ብለው ሀሳብ አቀረቡ፡፡
በመጨረሻም አርዮስን እና መንፈቀ አርዮሳውያንን በማውገዝ ወልድ በባሕርይው ከአብ ጋር አንድ ነው ብለው አጽድቀዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም 7 አንቀጽ ያለው ‘በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን’ እስከሚለው ድረስ ያውን የሃይማኖት መግለጫ አዘጋጁ፡፡
ከዚህም ባሻገር፡-
የትንሳኤ በዓል መቼ መከበር እንዳለበት ተወሠነ፡፡
ቀድሞ ምዕራባዊያን Dec -25 ልደቱ ታህሣስ -29 በምስራቅ ሲሆን ፋሲካ ግን ቀኑ የተወሠነ ባለመሆኑ ሚያዚያ- 14 በማናቸውም ቀን ቢውል (የአይሁድ ፋሲካን መሠረት በማድረግ) ይከበር ነበር እነዚህም Quarto Decmians (ባለ 14ኛ ቀናት) ተብለው ይጠሩ ነበር፡፡
የጉባኤው ውሳኔ ፡- ከሚያዚያ 14 በኋላ በሚውለው እሁድ እንዲከበር ይህንንም የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን እንድታሳውቅ
ሜሊጢያስ መለያየት ፡-
በዲዮቅልጢያኖስ ስደት ምክንያት የተሠወረው (ስደቱን ሽሽት) ጴጥሮስ (ተፍጻሜተ ሰማዕት) ጊዜ ሜሊጢዮስ በእስክንድርያ ጣልቃ በመግባት (ያለ ክልሉ) ኤጲስ ቆጶሳትን ሕግ በመተላለፍ መሾም ጀመረ፡፡ አንዳንዶችንም አወገዘ ፤ ጴጥሮስ ከተሠወረበት ሲመጣም ሜሊጢየስን አወገዘው፡፡ እርሱ ግን ይቅርታም ሳይጠይቅ ሥራውን ዝም ብሎ ቀጠለ፡፡ በዚህም ምክንያት ውዝግቡ እና ፀቡ እስከ ኒቂያ ጉባኤ ድረስ ቀጥሎ ነበር፡፡
ጉባኤውም ሰላም ለማውረድ 29 የሜሊጢየስን ጳጳሳት ሹመታቸውን ቢቀበልም በኋላ ላይ ከአርዮሳውያን ወግነዋል፡፡
ጉባኤው በተጨማሪም በስደት ጊዜ ሃይማኖታቸውን የቀየሩ ኦርቶዶክሳዊያንን በንስሐ እና በጥምቀት መልሷል፡፡
ሌሎች ጉዳዮች
እራስን ጃንደረባ ማድረግን መከልከል
ለንዑስ ክርስትያኖች የአመክሮ ጊዜ
አንድን ጳጳስ ለመሾም ሦስት ጳጳሳት መኖር እንዳለባቸው
የቅዱስ ቁርባን ተቀባዮች ቅደም ተከተል – ጳጳስ ፣ ካህን ፣ ዲያቆን …..
ስግደት ፡- በቅዳሴ ሰዓት ፣ በሰንበት ፣ በበዓለ አምሳ እንደማይገባ ጉባኤው ወስኗል፡፡
ድኅረ ኒቂያ ጉባኤ
በ 328ዓ.ም የእስክንድርላ ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ ከዚህ ዓለም በሞት ስለተለየ በእርሱ ምትክ የኒቂያ ጉባኤው ሻምፒዮን ቅዱስ አትናቲዮስ በሊቀ ጳጳሱ ኑዛዜ እና በመላው ሕዝብ በሙሉ ድምጽ የእስክንድርያ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ሆኖ ተሾመ፡፡
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አባ ሰላማም (ከሳቴ ብርሃን) በዚህ ወቅት ነበር ለኢትዮጵያ ተሹሞ የመጣው
አርዮሳዊያን ተቃውሞአቸውን ከበፊቱ አስበልጠው አጠንክረው የቀጠሉ በመሆኑ እስከ እለተ ሞቱ ሲታገላቸው ኖሯል፡፡ ለዚህም በመላው ሕዝበ ክርስቲያን ‘ታላቁ አትናቴዎስ’ (Atnatisus the Great) በመባል ይታወቃል፡፡
ከአርዮሳውያን ጋር በሚያደርገው ትግል ብቻውን የሆነ ያህል የነበረበት ጊዜ ስለነበረ (አርዮሳውያን በጣም ከማየላቸው የተነሣ) ‘ዝም ብለህ ነው የምትደክመው አንተ እኮ ብቻህን ነህ ዓለም በሙሉ ከእኛ ጋር ነው’ ተብሎ ሲዘበትበት ያለው ነገር “አንድ ብቻዬንም ሆኜ ዓለምን እቃወማለሁ ብቻዬንም እታገላችኋለው›› ያላቸው ሲሆን ያን ያህል ብዙ ተከታይ ማፍራት ችለው እንደነበር ያሳያል፡፡
አርዮሳውያን ከንጉሡ ጋር በመወዳጀት እንዲሁም አርዮሳውያንን የሚደግፍ ንጉሥ በተነሣ ወቅት ሁሉ በተደጋጋሚ ቅዱስ አትናቴዎስን ከመንበሩ አባርረው የሕዝቡን ተቃውሞ ሁሉ ቸል በማለት አርዮሳዊ የሆነ ጳጳስ ሲሾሙ ነበር፡፡
አትናቴዎስንም በተለያዩ ወንጀሎች እየከሰሱ ከነገሥታቱ ሊያጣሉ ሲሞክሩ ኦርቶዶክሳዊ ንጉስ ወይም ለዘብተኛ ንጉሥ ሲሾም ከተደበቀበት ወደ መንበሩ እየተመለሠ ሲከፋም እየሸሸ ወይም እየተያዘ እየተጋዘ(እየታሠረ) ለ 46 ዓመታት ጳጳስ ሆኖ ሲቆይ ከእነዚህ ዓመታት ውስጥ 15 ቱን ዓመታት ያሳለፈው በግዞትና በስደት ነበር፡፡ ይህም 5 ጊዜ በተደጋጋሚ ለስደት እና ለግዞት ተዳርጓል፡፡
በእነዚህ ዓመታት አርዮሳዊ የሆነ ጳጳስ ተሹሞ ለኢትዮጵያዊያን አባት አርዮሳዊ ጳጳሽ ለመሾም ደብዳቤ የጻፈ ቢሆንም የወቅቱ ነገሥታት ጥያቄውን ሳይቀበሉ ቀርተዋል፡፡
ቅዱስ አትናቴዎስ ‘ቅዱስ እንጦስ’ የሚለውን የመጀመሪያውን መነኩሴ አባት ታሪክም የጻፈው በዚህ ወቅት በስደት እያለ ነበር፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ቅዱስ አትናቴዎስ
Againest Ariars (ለአርዮስ መልስ)
Againest The Athen (ለአሕዛብ መልስ) እና
ብዙ ደብዳቤዎችን በዘመኑ ጽፏል፡፡ በታላቅ ስራዎቹም ምክንያት አትናቴዎስ ሐዋርያዊ በመባል ይታወቃል፡፡
የአርዮስ ሞት ፡- አትናቴዎስ በስደት እያለ አርዮስ ከክህደቱ ተመለስ በሚል ጓደኞቹ በእስክንድርያ ታላቅ አቀባበል አድርገውለት በቁስጥንጥያ ከሊቀ ጳጳሱ ጋር እንዲቀድስና በሕዝቡ ዘንድ ተቀባይነት እንዲያገኝ ለማድረግ ሲዘጋጅ የሆድ ህመም ተሰምቶት መፀዳጃ ቤት ሲሄድ በዛ ሆዱ ተዘርግፎ ሞተ፡፡
ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ምንም እንኳን ለቤተክርስቲያን ነጻነትን የሰጠ እና ብዙ እገዛ ያደረገ ቢሆንም የሃይማኖት ሰው አልነበረም እና ኃይል ወደ አመዘነበት እያጋደለ በስተመጨረሻም ወደ ክርስትና የሚያስገባውን ጥምቀት የተጠመቀው በሞት አፋፍ ላይ በነበረበት ወቅት በአርዮሳዊው ወዳጁ እጅ ተጠመቆ ነው፡፡

Please follow and like us:
error0
fb-share-icon20

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Related Post

አንደኛው ዓለም ዐቀፍ ጉባዔ /የኒቂያ ጉባኤ/ (ሲኖዶስ) በ 325 ዓ.ም (ክፍል አንድ)

መንስኤው አርዮስ የሚባል ካህን የምንፍቅና አስተምህሮ ነው፡፡ መንስኤው አርዮስ የሚባል ካህን የምንፍቅና አስተምህሮ ነው፡፡አርዮስ ፡- በ 260 ዓ.ም በሊቢያ ከግሪካዊ ክርስቲያን ቤተሰብ ተወለደ፡፡በእስክንድርያም በአንጾኪያም በከፍተኛ ደረጃ የመጽሐፍቶችን የስነ መለኮት ትምህርት

አርዮሳውያንን አልቀበልም በማለቱ በመንግስት ዛቻ የደረሰበት ቅዱስ አባት

ቅዱስ ባስሊዮስ በ329 ተወልዶ በ379 በ50 ዓመቱ ከዚህ ዐመት እንግልት በእረፍት ተለየ፡፡ ቅዱስ ባስልዮስ በዐለማዊ ትምህርቱ ከቅዱሳን አባቶቹ ሁሉ ቀዳሚውን ቦታ የሚይዝ ሲሆን በመንፈሳዊ ሕይወቱ እና እውቀቱም የመነኩሴ ሊቅ እና

አርዮስ እንዴት ሞተ

ይህ መልእክት ቅዱስ አትናቴዎስ ለግብጽ ጳጳሳት እና በአንድ ወቅት ለእስክንድርያ ትምህርት ቤት የበላይ ለነበረው ለቴሙሱ ቅዱስ ሴራፕዮን የጻፈው ነው፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ይቀጥል፤ የአርዮስን የአሟሟት ሁኔታ እንድገልጽላችሁ ጠይቃችሁኝ ነበር……….በሱ ሞት የምደሰት